Thursday, March 29, 2012

ማኅበረ ቅዱሳን ከሰሞኑ በሃይማኖት ሽፋን የአገራችንን የፖለቲካ አየር ለመበከል ያደረገው ጥረት እንዳልተሳካለት ተገለጸ


ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ መለያዎችን ለብሶ እንደአየሩ ሁኔታ ሲጫወት የቆየውና በዚህ በአቢይ ጾም ህዝቡ በተለይ ስለ ዝናብ እጥረት እግዚኦ እያለ ባለበት ወቅት ፖለቲካዊነቱ አይሎበት በተቃዋሚ ፖለቲከኛነት የተገለጠውና በሃይማኖት ሰበብ አገርን ለማመስና ኦርቶዶክሳውያንን በመንግስትና በቤተክህነት ላይ ለማነሳሳት ዘመቻ የጀመረው ማህበረ ቅዱሳን፣ በአሜሪካ የሚገኙ ካድሬዎቹን ከማሰለፍና በድረገጾቹ ላይ የጦርነት ነጋሪት ከመጎሰም ያለፈ ትርፍ እንዳላገኘ በአገር ውስጥ ያለው ሁኔታ ይመሰክራል።

በዋልድባ ገዳም አካባቢና የገዳሙ ይዞታ ባልሆነው ቦታ ላይ ሊሰራ የታቀደውን የስኳር ልማት ፕሮጀክት በመቃወምና በዝቋላ ተራራ ላይ ከበጋው ደረቅ የአየር ንብረት ጋር በተያያዘ የተነሳውን ሰደድ እሳት ምክንያት በማድረግ ክስተቶቹን ፖለቲካውን ለማስተዋወቅና ተከታይ ለማፍራት እየተጠቀመበት መሆኑን እየታዘብን ነው። በዋልድባ ገዳም ውስጥ ሰርገው ከገቡ የቀበሮ ባህታውያን ፖለቲከኞች ጋር ማህበሩ ያለውን ግንኙነት አሜሪካ ካሉት ወኪሎቹና ስውር አመራሮቹ ጋር በማቀናጀት የጀመረው ሰላማዊ ሰልፍ ብዙዎችን አስገርሟል። አንድአድርገን የተባለው የማህበረ ቅዱሳን ድረገጽ
ዋልድባ ሲመታ  ዝቋላ አለቀሰ፣
እኔ አላማረኝም-ይሄ አገር ፈረሰ።
ዋልድባ ሲታመስ-ዝቋላም ነደደ፣
እኔ ፈርቻለሁ- ይሄ አገር ታረደ።
በሚል ህዝቡን ለመቀሰቀስ የተጠቀመበት የክተት አዋጅ ማህበሩ በፖለቲካ መስከሩንና በዋልድባና በዝቋላ ስም አጋጣሚውን ለፖለቲካ ፍጆታው ለመጠቀም እየተራወጠ መሆኑን ያሳያል፡፡ በዋልድባ አካባቢ ሊሰራ ታቀደው የስኳር ልማት ፕሮጀክት የገዳሙን ክልል ያልነካ መሆኑን፣ ከገዳሙ ሰርጎገብ ፖለቲከኞችና ከማህበረ ቅዱሳን በቀር የገዳሙ መነኮሳት፣ የአካባቢው ተወላጆች፣ የመንግስት አካላትና የቤተክህነት ተወካዮች ባሉበት በተደረገ ውይይት የተረጋገጠ ነው፡፡ እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ በዋልድባ አካባቢ በመንግስት የታቀደው የልማት ስራ ቢሰራአገር ፈረሰያሰኛል ወይ? ይህ አይን ያወጣ ፖለቲካ እንጂ ሃይማኖተኛነት አይደለም፡፡ ደግሞስ የዝቋላ ተራራ በበጋው የአየር ንብረት ሳቢያ ቢቃጠልአገር ታረደያሰኛል ወይ? መንግስት ተራራውን በማቃጠል ምን ይጠቀማል? በዚህ የሚያገኘው የፖለቲካ ትርፍ አል ብሎ ማሰብስ ይቻላል ወይ? ይህ በፍጹም የማይታሰብ ነገር ነው፡፡ እንደዚህ አይነት አደጋ በአገራችን ብቻም ሳይሆን በሌሎችም አገሮች ይከሰታል፡፡ አደጋው ተፈጥሮኣዊ እንጂ መንግስት ሆን ብሎ ያደረሰው ነው ማለት የማያስኬድ ነው፡፡ አሁን በአገራችን በአብዛኛው የበልግ ዝናብ እጥረት አለ፤ ሙቀቱም ከፍተኛ ነው። ለዚህም መንግስትን ተጠያቂ ሊሆን ነው? ይህ በጣም አስቂኝ ነው። ስለዚህ በሃይማኖት ካባ የምታደቡ ፖለቲከኞች ሆይ እጃችሁን ከቤተክርስቲያናችን ላይ በማንሳት በፖለቲካ መለያችሁ ብቻ ጨዋታውን ብትጫወቱ የተሻለ ነው።

ማህበሩ በፖለቲካ ሰክሯል የተባለው በመላምት አይደለም፡፡ በየድረገጹ እየጻፋቸው የሚገኙ ጽሁፎቹ ፖለቲካዊ እንጂ ሃይማኖታዊ መዓዛ የራቃቸው በመሆናቸው ነው፡፡
ክርስቲያኖች በአላውያን ነገስታት ወይም በእምነት የለሽ ገዢዎቻቸው ጭቆና ሲበዛባቸው በጸሎት አምላካቸውን ከመማጸን በተጨማሪ ድምጻቸውን ለመንግስታት ማሰማት በአሐት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድየተለመደ ነው:: የግብጽ፣ የአርመን እና የሶርያ ክርስቲያን ወንድሞቻችን በተለያዩ ጊዜያት በገዢዎቻቸው ጭቆናሲደርስባቸው ለዓለም መንግስታት እና ለራሳቸውም መንግስታት በአቤቱታ ሰላማዊ ሰልፍ ጩኸታቸውን እንደሚያሰሙ በተለያዩ የዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ሲዘግቡ እንሰማለን:: በሕገ ክርስትና በኢ-አማኞችጭቆና ሲደርባችሁ የአቤቱታ ሰላማዊ ሰልፍ አትውጡ የሚል ነገር የለም:: ስለዚህ ክርስቲያኖች የአቤቱታ ሰላማዊ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣታቸው ተገቢ ነው::ሲል አሐቲ ተዋህዶ የተባለው ሌላው የማህበሩ ድረገጽ ጽፏል። 

ይህ ጽሁፍ የሃይማኖት ካባ የደረበ መስሎ ከመቅረቡ በቀር ፖለቲካዊ ጽሁፍ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ክርስቲያኖች በዓለም ሲኖሩ መብታቸው መገፈፍ የለበትም፡፡ መብታቸውንም ማስከበር አለባቸው፡፡ ሃይማኖታዊ መብታቸውን የሚያስከብሩት ግን በሰላማዊ ሰልፍ ጭምር ሳይሆን በእግዚአብሔር ፊት በጾም በጸሎት በመገኘት ነው። እኛ ከግብጻውያን ከሶርያውያን ከአርመናውያን ሳይሆን ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተማርነው ይህንን መንፈሳዊ ውጊያ ነው እንጂ ፖለቲካንም ሃይማኖትን እያጣቀሱ መሄድን፣ ድብቅ ፖለቲካዊ አጀንዳን በሃይማኖት ሽፋን ማቅረብን አይደለም። ውጊያችንም ከስጋና ከደም ጋር ሳይሆን ከክፋት መንፈሳውያን ሰራዊት ጋር ነው። ስለዚህ ማህበረ ቅዱሳን ሆይ በሁለት ቢላ መብላትህን አቁም፤ ወይ ሃይማኖቱን ወይ ፖለቲካውን ምረጥ።

ከዚህ ሁሉአገር ይያዝልንትርምስ ጀርባ የማህበረ ቅዱሳን እጅ እንዳለበት ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ በአገር ውስጥ በሚታተሙ የግል መጽሔቶች ላይ ፈራተባ እያሉ አስተያየት ሲሰጡ የነበሩት የማህበሩ ከፍተኛ ሰዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ ብርሃን አድማስ የተባለው የማህበሩ ሰው አዲስ ጉዳይ በተባለው መጽሄት ላይ ዋልድባን ጉዳይ አስመልክቶ የሰጠው አስተያየት የሚጠቀስ ነው። ይኸው ብርሐኑ አድማሴ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ  ሰልፍን የሚቀሰቅሰውን ፖስተር ማድረጉ የሚታወቅ ሲሆን ተጠያቂ በሌለባቸው ድረገጾቻቸው ላይ ግን ያለገደብ ህዝቡን ተነስ ሲሉ ነበር።  በውጭ ያለውን ሰላማዊ ሰልፍ ሲያስተባብሩ የነበሩት ደግሞ የዋሽንግተን ዲሲዎቹ የማህበሩ ሰዎች እነብርሃኑ ጎበና ናቸው።

No comments:

Post a Comment