Monday, March 26, 2012

አቡነ ሳሙኤል ቅድስት ስላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ውስጥ ሽምቅ ውጊያ መጀመራቸው ተሰማ


በጠቅላይ ቤተክህነት ግቢ ለጳጳሳት ማረፊያ በተሰራው ህንጻ ውስጥ ሳይሆን፣ ተምረው ባላለፉበት በቅድስት ስላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ቅጥር ግቢ የሚኖሩት የልማት ኮሚሽን የበላይ ጠባቂ አቡነ ሳሙኤል ከማህበረ ቅዱሳን የተሀድሶ መናፍቃንን ዘመቻ ለመከላከል በሚል ከሰበሰበው ገንዘብ ላይ እንደተለቀቀላቸው በሚታመነው ገንዘብ አንዳንድ የኮሌጁን ተማሪዎች በማባበልና ከብጹእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋር መልካም ግንኙነት አላቸው የሚባሉ ተማሪዎችን በመዋጋት በውስጣቸው ተዳፍኖ አልወጣላቸው ያለውን መፈንቅለ ፓትርያርክ እንደገና ለመሞከር ሽምቅ ውጊያ መጀመራቸው ተሰማ፡፡

አቡነ ሳሙኤል ከማህበሩ ጋር በመቀናጀት ለጀመሩት ሽምቅ ውጊያ አንዱ የቤት ስራቸው በኮሌጁ ውስጥ ከዚህ ቀደም በደጀሰላም ድረገጽ ላይ ወጥቶ የነበረውና ማህበረ ቅዱሳን ‹‹ተሀድሶ ናቸው ይባረሩልኝ›› ብሎ ያለባለቤትና አድራሻ የላከውንና በኮሌጁ አስተዳደር ውድቅ የተደረገውን ክስ እንደአዲስ ማንቀሳቀስና የተባሉትን ደቀመዛሙርት ከኮሌጁ ማስወጣት ነው፡፡ ከሰሞኑም ያው ስም አጥፊ ደብዳቤ እንደ ተለመደው ያለባለቤትና አድራሻ ተልኮ ለኮሌጁ አስተዳደር ከደረሰ በኋላ ፍሬከርስኪ ሆኖ በመገኘቱ ውድቅ ተደርጓል፡፡ ምክንያቱም ባለቤት የለውም አድራሻም የለውም፡፡

በዚህ የሽምቅ ውጊያ ኮሌጁን በማዳከሙ ተግባር በገንዘብ እየተገዙ ለተሰለፉት የበሉበትን ወጭት ሰባሪዎች፣ አድርባይ የውስጥ አርበኞችና ቅጥረኞች ለሆኑት ተማሪዎች አቡነ ሳሙኤል ዲኤስ ቲቪ እንዲገዙበት ከሁለት ብር በላይ እያደሉ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከሚጠቀሱት መካከልም 2 አመት ተማሪ የሆነው ሰለሞን፣ 4 አመቱ ደቀመዝሙርና የእግዚአብሔር አብ ቤተክርስቲያን ተቀጣሪ፣ 3 አመቱ አባ ዮሀንስ፣ 3 አመቱ ብርሀኑ፣ 3 አመቱ የቂርቆሱ በሀይሉ፣ ከወ/ ዘውዴና ከማንያዘዋል ጋር በመጣመር ማህበሩ ‹‹የአይናቸው ቀለም አላማረኝም›› ያላቸውን ደቀመዛሙርትና አገልጋዮች በፈጠራ ወሬ ከኮሌጁ ለማስባረርና ከአገልግሎት ለማሳገድ እየዶለቱ ይገኛሉ፡፡ አባ ሳሙኤልም 12/7/ 2004 . በስላሴ ኮሌጅ ውስጥ፣ ቸሬ፣ ወንድወሰን፣ ዳንኤል ግርማ (ዴራ) እና በስም ማጥፋት ወንጀል ጥፋተኛ ተብሎ በገደብ ከተለቀቀው ደስታ ጋር በዚሁ ጉዳይ ስብሰባ ተቀምጠው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከሁሉም በገደብ የተለቀቀው አቶ ደስታ ፍርድ ቤት ጥፋተኛ ብሎት ሲያለቃቅስ በቅጣት ማቅለያ በገደብ የለቀቀው መሆኑን ዘንግቶ አሁንም በሌላ ወንጀል ውስጥ ለመገኘት መሰለፉ ከትላንት ምንም እንዳልተማረና ነገንም አርቆ እንዳልተመለከተ ያሳያል፡፡
  
ከማህበረ ቅዱሳን ጋር በማበር ማህበሩ የሰጣቸውን ተልኮ ለመፈጸምና ጎን ለጎንም ማህበሩ የገባላቸውን የመጨረሻና ትልቅ ተስፋ (ፓትርያርክ መሆን) ለማሳከት ሽምቅ ውጊያ የጀመሩት አባ ሳሙኤል ከስላሴ ግቢ መልቀቅ እንዳለባቸው አንዳንዶች እየተናገሩ ነው፡፡ በስላሴ ኮሌጅ ውስጥ መሆን የመረጡት እንደ ጳጳስ ሳይሆን እንዳሻቸው ለመኖር ስለሚመቻቸው ነው የሚሉት እነዚሁ ታዛቢዎች፣ ይሄው ታውቆ የኮሌጁን ግቢ እንዲለቁ መደረግ አለበት ሲሉ ይናገራሉ፡፡

1 comment:

  1. ምንጭ ስትጠቕሱ ትክክለኛውን ምንጭ ለማጣራት ሞክሩ በደጀ ብርሀንም እንደተጠቀሰው ከአውደ ምሕረት ብሎግ የተወሰደ ነው http://awdemihret.blogspot.com/2012/03/blog-post_24.html

    ReplyDelete