Wednesday, May 9, 2012

በሀዋሳ አሥር የማይሞሉ ጥገኛ ነጋዴዎች አቡነ ገብርኤል ከቦታቸው እንዳይነሱ የድጋፍ ድምጽ በማሰባሰብ ላይ ናቸው ተባለ


የየአጥቢያ አስተዳዳሪዎችም ማመልከቻዎቻቸውን ፋክስ እንዲያደርጉ ተገደዋል ተብሏል

በሀዋሳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናንና የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር መካከል ለሁለት ዓመታት ያህል የዘለቀ ግጭት ሰፍኖ መቆየቱ ይታወሳል፡፡  በዚህም ግጭት አቡነ ገብርኤል ማኅበረ ቅዱሳንን ከላይ እስከ ታች ባሉ የቤተክርስቲያኗ አስተዳደራዊ መዋቅር ውስጥ ሰግስገው ያስገቡ ሲሆን፣ ባሳዩት የመልካም አስተዳደር ግድፈት በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ምዕመናንና ምዕመናት ከቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ ተባርረውና ተሰደው የሚገኙ መሆናቸውን የተለያዩ ብሎጎችና የዜና ምንጮች መዘገባቸው አይዘነጋም፡፡

አቡነ ገብርኤል በሀዋሳ ግጭት አፈታት ከቅዱስ ሲኖዶስ ልዩ ጽ/ቤት እና ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ በተለያዩ ጊዜያት የወጡ መመሪያዎችን፣ ትዕዛዛትንና ማሳሰቢያዎችን በመጣስ ግጭትን የሚያባብሱ እርምጃዎችን ሲወስዱ መቆየታቸውና ለሠላም የሚደረገውን ጥረት ሆን ብለው ሲያደናቅፉ እንዲሁም የዐዋቂ አጥፊ ሆነው ከዳንስ ቤቶች ባለቤቶችና አሥር ከማይሞሉ ጥገኛ ነጋዴዎች ጋር በማበር ንጹሐን ምዕመናንን ሲያስደበድቡና ሲያሳስሩ መክረማቸው በገሃድ የሚታወቅ ነው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ከአንድም ሦስት ጊዜ (ማለትም ግንቦት 2003 ዓ.ም፣ ጥቅምት 2004 ዓ.ም እንዲሁም ታኅሣሥ 2004) መደበኛና ልዩ አስቸኳይ ጉባዔ ጠርቶ በአቡነ ገብርኤልና በሀዋሳ ምዕመናን መካከል የቆየውን ግጭት ለመፍታት አጀንዳ ቢይዝም፣ አቡነ ገብርኤል ሆን ብለው ከጉባዔው መካከል ባለመገኘትና ግብረ አበሮቻቸው ደግሞ እርሳቸው በሌሉበት የእርሳቸውን ጉዳይ አናይም በማለት የምዕመናን ዕንባና ደም የትም ፈሶ እንዲቀር ፈርደውበታል፡፡

ይሁን እንጂ በአሁኑ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ተልዕኳቸውን የጨረሱ መሆናቸው ታውቆ አቡነ አብርሃምን በእርሳቸው ቦታ ላይ ለመተካት ጥረት በመደረግ ላይ ሲሆን፣ ጥገኛ ነጋዴዎቹ ደግሞ በበኩላቸው እርሳቸው ከሄዱብን ኦዲት የሚያደርገን ሊቀጳጳስ መጥቶ ጉዳችን ይወጣል፤ እንዋረዳለን ከሚል ስጋት በትላንትናው ዕለት ምሽት (ማክሰኞ ሚያዝያ 30 ቀን 2004 ዓ.ም) እርሳቸው እንዳይነሱባቸው በከተማዋ አጥቢያ ቤተክርስቲያናትና ልዩ ልዩ ሥፍራዎች በመሯራጥ የድጋፍ ድምፅ ለማሰባሰብ ጥረት በማድረግ ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡ (በነገራችን ላይ ጥገኛ ነጋዴዎቹ ከዚህ በፊት ምንም ያልነበራቸውና ከሀዋሳ ከቅዱስ ገብርኤል ገዳም በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ በመመዝበር ራሳቸውን ያደራጁ መሆኑ በብዙዎች ዘንድ ይታመናል፡፡ ከዚህም በላይ እነዚህ ጥገኛ ነጋዴዎች ቅን የቤተክርስቲያን አገልጋይ በመምሰል፣ ሰባት ያህል አጥቢያ ቤተክርስቲያናት በሰበካ ጉባዔ አባልነት፣ በልማት ኮሚቴና በበጎ አድራጎት ስም ተሰግስገው እዚህም፣ እዚያም ያለ አጥቢያቸው በመወራጨት የቤተክርስቲያኗን የመልካም አስተዳደር ገጽታ ያበላሹ መሆኑ በይፋ ይነገራል)፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘም የየአጥቢያ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪዎችም አቡነ ገብርኤል ከቦታቸው እንዳይነሱ ማመልከቻዎቻቸውን ፋክስ እንዲያደርጉ በእጅ አዙር የተገደዱ ሲሆን፣ አሥር ከማይሞሉት ጥቂት ነጋዴዎች መካከል ብርሃን እና አዳነ የተባሉ ግለሰቦች እዚህም እዚያም ተሯሩጠው የሸከሸኩትን ፊርማ አሰባስበው ሌሊቱን በመጓዝ ከጥሩ የእጅ መንሻ ጋር ጠቅላይ ቤተክህነት አባቶች ዘንድ ከተፍ ብሎ "የሀገር ያለህ"!! ብለው እንደለመዱት በሐሰት ለመጮኽና መሬት ላይ ለመንከባለል ዕቅድ መያዙ ተረጋግጧል፡፡ ይሁን እንጂ ለእነዚህ ጥገኛ ነጋዴዎችና ማኅበረ ቅዱሳን ምቾት ካልሆነ በስተቀር አቡነ ገብርኤል ማናቸውም ፀጉር የሚያስነጭ መንፈሳዊ ፍቅር፣ አገልግሎትና አርአያነት ያለው መንፈሳዊ ፍሬ የሌላቸው ናቸው (አራት ነጥብ)

በሰሞኑ የግንቦት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ሦስት ውጤት ይጠበቃል፡፡ እነዚህም፣
  1. አቡነ ገብርኤል በቦታቸው እንዲቆዩ ተደርጎ በያዙት የጥፋት ጎዳና የቤተክርስቲያን ሀብት እንዲመዘበር፣ ማኅበረ ቅዱሳን ራሱ ሃይማኖት ሆኖ እርሱ ያልፈቀደው ምንም ነገር እንዳይከናወን የፈላጭ ቆራጭ እና ሙስና የተንሰራፋበት ሥርዓት እንዲሰፍንና የተሰደዱት በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ምዕመናንና ምዕመናት እንደወጡ እንዲቀሩ መፍቀድ፣
  2. አቡነ ገብርኤል ለይስሙላ ከቦታቸው ተነስተው፣ እርሳቸው የዘረጉት በማኅበረ ቅዱሳን የደነበሸ አስተዳደራዊ መዋቅር ባለበት ቆይቶ እንደ አቡነ አብርሃምና አቡነ ሳሙኤል ያሉትን ቀንደኛ የማኅበረ ቅዱሳን አራማጆችን በቦታው በመተካት የአሥር ሺዎች ምዕመናንን ሰቆቃ ማብዛት በየወገኑ እንደፍላጎቱ እንዲበተን አድርጎ ከእናት ቤተክርስቲያኑ ጋር ያለውን ቁርኝት እስከመጨረሻው መበጠስ፣
  3. አቡነ ገብርኤል ከቦታቸው ተነስተው፣ ከማኅበረ ቅዱሳን ንክኪ ነፃ የሆነ ቅን እና በሳል መንፈሳዊ አባት መድቦ፣ የቤተክርስቲያንን አስተዳደራዊ መዋቅር ከማኅበረ ቅዱሳን ንክኪ በማፅዳት፣ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩት ስደተኛ ምዕመናንና ምዕመናት ወደ እናት ቤተክርስቲያናቸው ተመልሰው ሠላም የሰፈነበት የአምልኮ ሥርዓት መመሥረት፣ ናቸው፡፡

እግዚአብሔር መንፈሱን በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ አፍስሶ የሀዋሳ ምዕመናንና ምዕመናት ዕንባና ሰቆቃ ያበቃ ዘንድ በአቡነ ገብርኤል ምትክ በሳል፣ ቅንና መንፈሳዊ አባት መድቦ፣ የቤተክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር ከማኅበረ ቅዱሳንና ከጥገኛ ነጋዴ ፀድቶ፣ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ የሀዋሳ ምዕመናን ወደ እናት ቤተክርስቲያናቸው ተመልሰው፣ ሁላቸውም ሠላም የሰፈነበት ሥርዓተ አምልኮ ይፈጽሙ ዘንድ ለዚያ ያብቃቸው እንላለን፡፡

የአብ ፀጋ፣ የወልድ ቸርነት፣ የመንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን!!!
የፃድቃንና ሰማዕታት ረድኤታቸው፣ የመላዕክት ጥበቃና ምልጃቸው፣
የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነቷ ከእኛ አይለይ!!!
አሜን!!!

No comments:

Post a Comment